Monday, September 9, 2013

ኢትዮጵያዊ ሕልም



ባልሳሳት ከትላንት ጀምሮ ይመስለኛል Zone9ers (ዞን 9ኞች) “ኢትዮጵያዊ ሕልም፣ ኑ አብረን እናልም!” በሚል መሪ ቃል ወይም ሃሽታግ ብዙ ኢትዮጵያውያን በሚጠቀሙባቸው የማህበራዊ ድረ-ገጾች ማለትም ፌስቡክና ትዊተር አማካይነት ለአዱሱ ዓመት እናም ከዚያም ለጥቀው ላሉት ዓመታት ሀገራዊ ህልሞቻችንን እንድናጋራ ጥሩ ርዕስ አምጥተው ብዙ ኢትዮጵያውያን በተለይም በውጭ የሚገኙት ህልማቸውን እያጋሩን ይገኛሉ፡፡ እስካሁን ብዙ ህልሞች አንብቤያለሁ ደስ ሚሉ፣ የሚያሳዝኑ፣ የሚያስከፉ፣ ብሎም የሚያሳፍሩ ናቸው፤ ለማንኛውም የኔ ኢትዮጵያዊ ሕልም ይሄ ነው፡፡
ኢኮኖሚው
ሁሉም ኢትዮጵያዊ ሳይሳቀቅ ቢያንስ በቀን ሶስት ጊዜ መብላት እንዲችል፤
ሁሉም ኢትዮጵያዊ የኔ የሚለውና በኃላፊነት የሚወጣው ስራ እንዲኖረው (በግሉም ተቀጥሮም ሊሆን ይችላል)፤
የዘይት ዋጋ አስወድዶ የጤፍ ዋጋ ያስወደደውን ገበሬ የሚራገም ነጋዴ ጠፍቶ ሕዝብነቱ ሁሌም የሚታወሰው ነጋዴ እንዲፈጠር፣
ግብር ግዴታዬ ሳይሆን መብቴ ነው ብሎ የሚከራከር ነጋዴ ተፈጥሮ ማየት፣
የተፎካካሪዬ ማደግ ለኔ መበረታቻ ነው ብሎ የሚያስብ ነጋዴ እንዲኖር፣
መጦሪያዬን ፎቅ ልስራ ሳይሆን ብዙ ዜጎች የሚቀጥር ፋብሪካ ልገንባ የሚል ባለሃብት ማየት፣
እኔ በምከፍለው ግብር የሚሰራ የመንግስት ሰራተኛ በቅጡ ሊያስተናግደኝ መቻል አለበት ብሎ የሚያስብ እጁን ኪሱ ከመክተቱ በፊት፣
ፖለቲካው
የታሰሩ የፖለቲካ እስረኞችና ጋዜጠኞች ተፈተው በነጻነት ሲጽፉ፣ ሲቀሰቅሱ፣ ፓርላማ ገብተው ሲከራከሩ ማየት፣
ሁሉም የሚስማማበት ምርጫ የትም ዓለም ላይ ይደረጋል ብዬ አላስብም ነገርግን የኢትዮጵያን ሕዝብ በብዛት ያሳመነ ምርጫ ተደርጎ ተሸናፊው ቡድን አሸናፊውን እንኳን ደስ አለህ ብሎ ለህዝብ ጥቅም ሲል አብሮት የሚሰለፍበት ምርጫ ማየት፣
ሁሉም ኢትዮጵያዊ በሁሉም መስክ (ፖለቲካ፣ ኢኮኖሚ፣ ማህበራዊ ጉዳዮች)  እኩል ተጠቃሚነትና እኩል እድል ኖሮት ማየት፣
ዘርና ጾታ በተፈጥሮ የሚገኙ እንጂ በዕድል ወይም በአጥንት ወይም በዕውቀት የማይመጡ መሆኑን አውቆ በሁለቱ መገለጫዎች ምክንያትነት ብቻ የበላይ ነኝ ብሎ የማያስብና ከብሔሬ በፊት ኢትዮጵያ ትቀድማለች ብሎ የሚያስብና ኢትዮጵያ የኔ ናት የሚል ትውልድ ማየት፣
ነጻ ፕሬስ ኖሮ ለሕዝቡና ለሀገሪቱ ጠቃሚ የሆኑ ሀሳቦች እየወጡ የሚፋጩበት፣ ለእስኪሪፕቶን በእስኪሪፕቶ አንጂ በጥይትና እስር ምላሽ የማይሰጥባትን ኢትዮጵያ ማየት፣
ስልጣን ህዝብን ማገልገያ እንጂ ማስፈራርያ ብሎም የግል ጥቅም ማፍሪያ ያልሆነባትን ኢትዮጵያ ማየት፣
ተቃዋሚ ስለተባሉ ብቻ መንግስት የሚሰራውን በሙሉ መቃወም አለብኝ ብሎ የማያስብና የመሃል መንገድም አለ ብሎ የሚያስብ ተቃዋሚ ተፈጥሮ ማየት፣
ዳያስፖራ ፖለቲከኞች በሰንሰለት እንደታሰረ ኃይለኛ ውሻ ውጭ ሆናችሁ ወደ ቤት ከምትጮሁ እስኪ የሞቀ የውጭ ኑሯችሁን ከቻላችሁ ይዛችሁ ካልቻላችሁ እጃችሁ ላይ ያለውን ይዛችሁ ኑና እንታገልልሃለን የምትሉትን ሕዝብ በዕውቀታችሁና በገንዘባችሁ ችግሩን ፍቱለት፣ ችግር ሁሉ ስልጣን በመያዝ ብቻ አይፈታምና፡፡በጭፍኑ መንግስትን መቃወም ብቻ ለገዥው መንግስት ጥሩ የፕሮፖጋንዳ ግብዓት እየሆነ ስለሆነ መሬት ይዛችሁ መክራችሁበት ወደ ሀገራችሁ መጥታችሁ ወይም ባላችሁበት ለሀገራችሁ የምትችሉትን አርጋችሁ ማየት፣
መንግስት ለሕዝብ የሚጠቅም ፖሊሲና ስትራቴጂ ሊቀርጽ ሲያስብ ከፖለቲካ ባሻገር የመስኩን ልሂቃን እያማከረ የሚዘጋጅባት ኢትዮጵያን ማየት፣
ግንባርና ቀንድ እያሉ ጎጥ እየፈጠሩ ሀገርን የሚያክል ነገር እንደ አቡጀዲ ለመቅደድና ለመገንጠል የሚያስቡ ኃይሎች በጠረጴዛ ዙሪያ ቁጭ ብለው በሰለጠነ ሰው ስረዓት ሲነጋገሩ ማየት፣
ማህበራዊ ጉዳዮች
ሃይማኖት የፖለቲካ መጠቀሚያ መሳሪያ ሳይሆን ህዝብን ግብረ ገብነት ማስተማሪያ ሆኖ ማየት፣
የእምነት ተከታዮች በጎሪጥና በጥላቻ የሚተያዩባት ሳይሆን አንዱ ለሌላው የወንድሜን ሃይማኖት አትኩበት ብሎ ለጎረቤቱ ዘብ የሚቆምባት ኢትዮጵያን ማየት፣
ሌላው በሰራው ጀግንነት ቁጭ ብሎ የሚኩራራ ትውልድ ሳይሆን ለታሪኩ ክብር ሰጥቶ ካለፈው ጥሩውንም መጥፎውንም መርምሮ የሚማር ትውልድ ተፈጥሮ ማየት፣
የራሱን ታሪክ ለማጉላት ብሎ ያለፈውን የሚያጨፈግግ መንግስት ሳይሆን ካለፈው ስህተት ተምሮ ለመጭው ታሪኩ የሚጠነቀቅ ብሎም ባለፈው ታሪካችን ውስጥ ያበሩ (ብልጭ ያሉ) መልካም ጅማሮውችንና ታሪኮችን አክብሮ ለትውልድ ማስተላለፍ፣
እያለ እያለ መልካም መልካሙን ተመኘሁ እናንተስ?

Tuesday, August 27, 2013

ስለ በግ ጥሩነት ለማውራት ፍየልን ማንቋሸሽ!?

"ጎበዝ!ይሄ ሰርክ በኢቲቪ እና በመንግስት ራድዮናዎች ላይ ያሉት ትንታግ ካድሬዎቻችን የሚሰብኩን እና ወቅት እና ሁኔታዎችን ጠብቀው ወደ ቴሌቭዥናችን መስኮት ብቅ የሚሉት እነዛ የኢቲቪ "አንዳንድ የከተማው ነዋሪዎች" የሚምሉበት፣ ቃል የሚገቡበት ጠቅላይ ሚኒስትሩ ራዕይ ጉዳይ እየቆየ ሲመጣ ያሳስበኝ ጀምሮአል። እያሳሰበኝ ያለው ግን በፀረ ሰላም እና በፀረ ልማት ሀይሎች የሚደርስበት ተፅፅኖ ሳይሆን ይሄ ራዕይ በኔ ዕይታ ታሪክን በማዛባት ላይ እየፈጠረ ያለው ተፅፅኖ ነው። በተለይ ኢቲቪን አዘውትረው የሚከታተሉ እና ስለ ሀገራቸው የቀደመ ታሪክ የማንበብ ወይም የማወቅ እድል ያልተፈጠረላቸው ብላቴኖች በሀገራችን አሁን እየታዪ ያሉ ማህበራዊ እና ኢኮኖሚያዊ ለውጦች በታሪካችን ለመጀመሪያ ጊዜ የታሰቡ፣ የተወጠኑ እንዲሁም ከ1983 በፊት የነበሩት መሪዎች ሀገራቸውን ለማዘመን ምንም ያልጣሩ፣ እንዲሁም ከድህነት ለማውጣት ምንም ያልሞከሩ ቢያንስ እንኩዋን ራዕዪ ያልነበራቸው የሚመስላቸው ይመስለኛል። አሁን እንዲህ ስል ደግሞ የቀድሞው ጠቅላይ ሚንስትራችን የነበራቸውን ቁርጠኝነት እና የሰሩዋቸውን ስራዎች ማንኩዋሰሴ አይደለም። ስለዚህ ለማይረባ የፖለቲካ ትርፍ ታሪክን ባታዛቡ መልካም ይመስለኛል። ምናልባት እዚህ ጋር ታሪክን ማዛባት የሚለው ነገር አልከበደም የሚል ጥያቄ ሊኖር ይችላል፤እንደኔ እምነት ከብዙ የታሪክ ገፆች መሀል የወደዱትን ማግዝፍ ያልወደዱትን ደግሞ እስከነመፈጠሩ መርሳት ታሪክን ማዛባት ነው። ስለ በግ ጥሩነት ለማውራት ፍየልን ማንቁሸሽ አያስፈልገንም በግ ብቻዋን መቆም ትችላለች እና።የኔ ስሜት የብቻዬ ይሆን ወይስ እናንተም ታዝባችሁታል? አስተያየታችሁን ጣል አድርጉ::

ኤፍሬም አፈወርቅ

Wednesday, August 21, 2013

THE CREATION By Kahlil Gibran



THE CREATION
By
Kahlil Gibran

The God separated a spirit from Himself and fashioned it into Beauty. He showered upon her all the blessings of gracefulness and kindness. He gave her the cup of happiness and said, "Drink not from this cup unless you forget the past and the future, for happiness is naught but the moment." And He also gave her a cup of sorrow and said, "Drink from this cup and you will understand the meaning of the fleeting instants of the joy of life, for sorrow ever abounds."
And the God bestowed upon her a love that would desert her forever upon her first sigh of earthly satisfaction, and a sweetness that would vanish with her first awareness of flattery.
And He gave her wisdom from heaven to lead to the all−righteous path, and placed in the depth of her heart and eye that sees the unseen, and created in her an affection and goodness toward all things. He dressed her with raiment of hopes spun by the angels of heaven from the sinews of the rainbow. And He cloaked her in the shadow of confusion, which is the dawn of life and light.
Then the God took consuming fire from the furnace of anger, and searing wind from the desert of ignorance, and sharp−cutting sands from the shore of selfishness, and coarse earth from under the feet of ages, and combined them all and fashioned Man. He gave to Man a blind power that rages and drives him into a madness which extinguishes only before gratification of desire, and placed life in him which is the spectre of death.
And the God laughed and cried. He felt an overwhelming love and pity for Man, and sheltered him beneath His guidance.

From the Book: A Tear and a Smile

Friday, July 19, 2013

Tower in the Sky by Hiwot Teffera



ሰላም እንዴት ናችሁ? የተከበራችሁ የዚህ ጦማር ታዳሚዎች፡፡ እንዳለመታደል ሆኖ በተከፈተ ባጭር ጊዜ ውስጥ የምሰራበት መስሪያ ቤት የICT ባለሙያዎች በመስሪያ ቤቱ ሰራተኞች በተደጋጋሚ የሚጎበኙ፣ የስራ ጊዜን የሚሻሙ፣ ጸረ-መንግስት የሆኑ፣ ለስራ አላስፈላጊና የወሲብ ድረ ገጾች ተብለው ከተመደቡት እንደነ Facebook, Twitter, Addisnegeronline, Aigaforum, etc… ተርታ የኔም ብሎግ ተመድቦ ታግዶ/Blocked ይገኛል (ባለኝ ስታትስቲክስ መሰረት ብዙዎቹ የጦማሩ አንባቢዎች ከምሰራበት አካባቢ ናቸው)፡፡ የመጥፋቴም ምክንያት ይህና ሌሎች ከስራ ጋር የተገናኙ ምክንያቶች ያስከተሉት ስለሆነ ከልብ ይቅርታ እየጠየቅሁ ለአጋጆቼም ምቀኛ አታሳጣኝ እላለሁ፡፡
“Tower in the Sky” የሚል አዲስ አበባን ያነጋገረና እያነጋገረ ያለ መጽሐፍ ብዙ ሰምታችሁ ወይም ምንም አልሰማችሁ ይሆናል ነገር ግን አንድ ነገር በርግጠኝነት መናገር የምችለው መጽሐፉ እጅግ በጣም የሚገርም የአጻጻፍ ስልትን የተከተለ፣ ከፊልም በላይ ግልጥ አርጎ የሚያሳይ፣ በሙሉ ቅንነትና ሀቀኝነት የተጻፈ፣ ለማመን በሚያስቸግሩ ክስተቶችና ታሪኮች የተሞላ፣ በ1960 እና 70ዎቹና የነበረውን ትውልድ (በተለምዶ “ያ ትውልድ” የሚባለውን) አስተሳሰብ፣ አመለካከት፣ አካሄዶች፣ ስህተቶች፣ ጥንካሬዎችና ድክመቶች ነቅሶና አጥርቶ ያወጣ፣ እንዲሁም እውነት እንደሆነ በሁሉም ባለድርሻዎች የተመሰከረለት እጅግ እጅግ በጣም ድንቅ መጽሐፍ ነው፡፡
መጽሐፉ በሕይወት ተፈራ በእንግሊዘኛ ቋንቋ ተጽፎ በአዲሰ አበባ የኒቨርሲቲ ፕሬስ የታተመ ሲሆን በ437 ገጾች ለየት ያለ ግለ-ታሪክና ስለ ዘመኑና የጸሓፊዋን ምልከታ (Impression) ይተርካል፡፡ መጽሐፉ የባለ ታሪኳን የሕይወት ጉዞ ከዘናጭና ፈታ ያለች ፍሬሽ የዩኒቨርሲቲ ተማሪነት እስከ መካከለኛ የኢሕአፓ (የኢትዮጵያ ሕዝቦች አብዮታዊ ፓርቲ) አመራር/ አባልነት ያለውን አስፈሪ፣ አደገኛ፣ ሚስጥራዊ፣ በጀግነትና በእድል የተሞላ ታሪክ ያስነብባል፡፡
ሕይወት በመጽሐፏ አራት አስርት አመታትን ወደ ኋላ ወስዳ የነበራትን የፓለቲካ ንቃተ ህሊና፣ ለፓርቲዋ (ኢሕአፓ) እና ለአይዲዎሎጂው (ሌኒኒስት/ማርክሲስት) የነበራትን ታማኝነትና ፅናት ይዳስሳል፡፡
ሕይወት እንደማንኛውም ሐረር የተወልደ ልጅ ዘና ያለች መሳቅ መጫወት የምትወድ ባጭሩ ጣጣና ጭንቅ የሌለባት ወጣት ነበረች አዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ ገብታ ጌታቸው ማሩ የሚባል ወጣት ተዋውቃ ህይወቷን ባላሰበችው አቅጣጫ እስኪቀይረው ድረስ፡፡ ጌታቸው ማሩ በወቅቱ የአምስት ኪሎ የምህንድስና በውጤቱ ስመጥር ተማሪ፣ የተማሪዎች ፕሬዝደንት የነበረ፣ እጅግ በጣም አንባቢ፣ የአብዮት ኋላ ኢሕአፓ የሆነው ፓርቲ መስራች አባል ነው፡፡
ባጠቃላይ “Tower in the Sky” ያለፈውን ትውልድ ትክክለኛ ታሪክ ያስቀመጠ ነው፡፡ ከሁሉም በላይ ደግሞ አሁን ድረስ መሰረታዊ የሀገሪቷ ችግር የሆነውን ያለመደማመጥ ችግርና ጉዳቶቹን ቁልጭ አርጋ አመላክታለች፡፡ በመጨሻም ሕይወት በቁስ ለመተመን ፈጽሞ የማይቻልና ለትውልድ ቅርስ የሆነውን ይህንን ስጦታ በቅንነትና በነጻነት ሰርተሽ ስላበረከትሽ እጅግ የከበረ ምስጋና ይገባሻል፤ የጌታቸው ማሩን ታሪክ ብቻ ሳይሆን የትውልዱንና የሀገሪቷን ታሪክ ነው የጻፍሽው፡፡
  
ፍሬዘር ማሩ

Thursday, May 16, 2013

ዩኒቨርሲቲዎቻችን ድሮና ዘንድሮ

ይህን ርዕስ የመረጥኩት ፌስቡክ (ገጸ-መጽሀፍ ይለዋል አንድ ወዳጄ) ላይ በብዙ ሰዎች ሼርና ላይክ የተደረገውን ከዚህ በታች የሚገኘውን ፎቶ ከተመለከትኩ በኃላ ነው፡፡ የምስል ቅንብሩ የደብተራው ጸጋዬ እንደሆነ ምስሉ ላይ ይገልጻል፡፡ ከዚህ ቀጥሎ የጻፍኩትን አንብባችሁ የፈለጋችሁትን በሉ፡፡
“የድሮ ተማሪ ጥያቄዎች” ተብለው የተጠቀሱት
1.    መሬት ለአራሹ፡- ይህ ጥያቄ በጣም ትክክልና ወቅታዊም እንደነበረ አምናለሁ አንብቤ ከተረዳሁት፡፡ ግን በአሁኑ ወቅት መሬቱን የያዘው በብዛት ማለት ይቻላል በተለይ ሳኡዲ ስታር ሳይመጣ እራሱ እራሹ ነው፡፡ የሚያርሰውም ለግሉ ነው እንጂ ለ“ነፍጠኛው ገዥ መደብ አይደለም” (ት.ያ. (ትንሽ ያስቃል)) ስለዚህ ይህን ጥያቄ በዚህ ሰዓት ከማንሳት ኮብልስቶን መፍለጥ ይሻላል፡፡
2.   የምርጫ ድምፃችን ይሰማ፡- ሲጀመር ይሄ ጥያቄ በምን ቀመር የድሮ ተማሪዎች ጥያቄ ሊሆን እንደቻለ አልገባኝም፡፡ ምክንያቱም የድሮ ተማሪ የተማሪ ተወካይ ከመምረጥ ሌላ የምን ምርጫ ያርፋል? ሲቀጥል ጥያቄው የተጠየቀው በምርጫ 97 ወቅት ነው፣ ምላሹም “በለው ማን አንሳ አለው?” ሆኖ ያሁሉ ወጣት ሲሞት፤ አካል ጉዳተኞች ሲሆን፣ በጣም ብዙዎች ደግሞ ሲጫሩ (እዚህ ላይ በዛ ወቅት የተባረሩ ተማሪዎች የትም ሲቀሩ አባከና የሚላቸው አጥተው ያባረራቸው መንግስት ራሱ መልሶ ጸጸት ልባቸውን ስለመዘመዘው በኮብልስቶን ጠረባ ላይ እንዲሳተፉ ፈቀደላቸው (ት.ያ)) ዞር ብሎ የት ወደቁ ያለ ማነው፡፡ ስለዚህ የዛኔ በአደባባይ ወንድሙ ሲገደል፣ አካል ጉዳተኛ ሲሆን፣ ዝዋይና ዴዴሳ ሄዶ እሬቻውን ሲበላ ማንም ዞር ብሎ እንዳላየው እያየ ለምን አርፎ አይማር፡፡ ደግሞ አሁን እንደ ድሮው ሄዶ መምረጥ ቀርቷል አሉ በማርያም እየተባለ እየተደወለ እየመረጠ ለምን ይቃወም፡፡ ይልቅ በበቀደሙ የአካባቢ ምርጫ እለት ካርድ የወሰዱት ሰዎች ጋር ሲቆዩ ይደወል ነበረ መሰለኝና አንዱ ሰውዬ አስቸኳይ ስራ ስለነበረበት ቢሮ ገብቶ እየሰራ ደወሉለት ከዛ “እሺ መጣለሁ ትንሽ ስራ በዝቶብኝ ነው” ይላቸዋል፣ አንድ ሰዓት ቆይተው ደግመው ይደውላሉ “አሁንም ስራዬን አልጨረስኩም በቃ እስከ ማታ ስለሆነ ወደ 11፡00 ሰዓት ላይ መጥቼ መርጣለሁ” ይላቸዋል፣ ይሄኔ ደዋዩ ልጅ ከላይ ትዕዛዝ ተሰጥቶት መሰለኝ ምን ቢል ጥሩ ነው “ካልተመቾት ይንገሩንና ኮሮጆ ይዘን መጥተን ባሉበት እናስመርጦት” አለው፡፡ እናቴ ትሙት ኮሮጆ ይዤ ልምጣ ሳይሆን መጥተን ፒክ እናርጎት ነው እንጂ ያለው ሌላውን እውነቴን ነው ካላመናችሁኝ የነገረኝን ሰውዬ ላገናኛችሁ፡፡
3.   አንድ ሀገር አንድ ህዝብ፡- እውነት ለመናገር ፌደራሊዝም አሁን ባለው ሁኔታ ኢትዮጵያዊነት አዲስ አበባ ላይ ብቻ እንዲሆን አድርጎታል ብል ያመዋል እንዴ የሚለኝ ሰው እውነቱን ነው ከሚለኝ ያንሳል ብዬ አስባለሁ፡፡ በርግጥ ሁሉም ዜጋ በራሱ ቋንቋ መማሩንና በራሱ ተወላጅ መተዳደሩን ከማንም በላይ ብደግፍም አንድ ሀገር ውስጥ እስከኖርን ድረስ ሁሉም ዜጋ በማንኛውም የሀገሪቱ ክፍል ተዘዋውሮ ቢሰራ አሪፍ ነበረ፡፡ ሳስበው ከአሁን በኋላ አሃዳዊት ኢትዮጵያ ትኖራለች የሚል ግምት ፈፅሞ የለኝም ስለዚህ ኢትዮጵያዊነትን ለማጠናከር ከአሁን በኃላ መሰራት አለበት ብዬ የማስበው እያንዳንዱ የዩኒቨርሲቲ ተማሪ በክረምት ወቅት ወደ ቀዬው ተመልሶ ድንጋይ ከሚያሞቅ (አብዛኞቻችን እንደዚህ ነን) ከተወለደበት አካባቢ ውጭ ሄዶ ህዝብ እንዲያገለግል ቢደረግ ልክ በደርግ ጊዜ ተጀምሮ እንደነበረው የኢትዮጵያዊነት ስሜት ይጎለብታል ብዬ አስባለሁ፡፡ ማለትም የኤልከሬውን ልጅ እንትጮ ልኮ ከህዝቡ ጋር እየኖረ እንዲሰራ ቢደረግ ነገ ተመርቆ ወደ አካባቢው ቢሄድ ስራ ላይከለክሉት ይችላሉ፡፡ ለነገሩ ይህን ሃሳቤን ፕ/ር አንድርያስ እሸቴ ሸገር ላይ ባረጉት ጨዋታ ጥሩ አርገው አብራርተውታል፡፡
4.   አካዳሚክ ነጻነት ይከበር፡- የአንድ ከፍተኛ የትምህርት ተቋም አካዳሚክ ነጻነት የሚረጋገጠው ተቋሙ የሚከተሉትን ነጥቦች በአካዳሚክ መሰረት (Academic Grounds) ላይ ሆኖ መወሰን ሲችል ነው፡-
a.    ማነው ማስተማር ያለበት/ ማስተማር የሚችለው
b.    ምን ማስተማር አለብኝ
c.     እንዴት ማስተማር አለብኝና
d.    ማንን መቀበል አለብኝ
ስለዚህ እነዚህን ጥያቄዎች በአግባቡ ለመመለስ ወይም የመመለስ አቅም ያለው የትምህርት ተቋም አሁንም ድሮም ኢትዮጵያ ውስጥ ያለ ስለማይመስለኝ ከሁሉም በላይ ደግሞ እኔና መሰሎቼ አካዳሚክ ፍሪደም ብትሉን ትፈላሰፋለህ እንዴ በል አርፈህ ነገ ከማን እንደምንሰራ (እንደምንኮርጅ) አስብ ስለሆነ መልሳችን ጥያቄውን ለማንሳት አንደፍርም፡፡ ምክንያቱም እንኳን እኛ ተማሪዎቹ መምህራኖቻችን አያርፉትማ በተለይ ደግሞ አዳዲሶቹ ዩኒቨርሲቲዎች ላይ ያሉት ጠቅላላም ሆነ አካዳሚክ ዕውቀታቸው ወፍ የለም፡፡
5.   ሀገር አትገንጠል፡- ካስተዋላችሁ አሁን ዩኒቨርሲቲ ያለው ወጣት አኮ ሀገር ከተገነጠለች ነው ነፍስ ያወቀው (የሚያስተውል ቀልብ ያለው ሲኖር አይደል) ስለዚህ ይሄንንም ጥያቄ አናርፈውም፡፡ “የዩኒቨርሲቲ ተማሪ እስከሆነ ድረስ ስለ ሀገሩ አንብቦ ነው መረዳት ያለበት” የሚል ካለ ደግሞ መጽሀፍ ከማንበብ መገንጠል የሚቀናው ተማሪ ስለሆነ መስሚያው ጥጥ ነው በተለይ አንብብ ለሚለው ሰው፡፡
6.  በዘርና ጎሳ አትከፋፍሉን፡- በዘርና ጎሳ ተከፋፍሎ የመጣ ተማሪ እንዴት ብሎ ነው አትከፋፍሉን የሚለው ደግሞ ካልተከፋፈልክ ከሁሉም ተገለህ ብቻህን ሜዳ ላይ ልታወራ ነው፡፡ ስለዚህ አርፈህ መመሳሰል ነው፡፡ የአዲስ አበባ ልጅ ከሆንክ ብቻ ነው የዘርና ጎሳ ነገር ብዙ የማያሰጨንቅህ ምክንያቱም ኢትዮጵያዊ ሆነህ ነዋ የምታድገው አንድ ቋንቋ አውርተህ፤ ስምህ የጀግና ወይ የመጽሀፍ ቅዱስ ወይ የቁርአን ወይ የፈረንጅ ነው በምን ትለያያለህ፡፡ ለዚህም ጥሩ ማሳያ የሚሆነኝ በቀድሞ ስሙ የንግድ ስራ ኮሌጅ (ኮሜርስ) በአዲሱ ደግሞ የንግድ ስራ ት/ቤት ነው፡፡ እዛ ድሮም ብዙ የክፍለ ሀገር ተማሪ አይገባም አሁንማ ጭራሽ የክፍለ ሀገር ተማሪ አይገባም የመጀመሪያ ምርጫው ካልሆነ (ዶርምና ካፌ ስለሌለው ነው) እና እዛ ሄዳችሁ ዘር፣ ጎሳ ምናምን ብትሏቸው መስሚያቸው ድፍን ነው (ከክፍለ ሀገር መጥቶ ፕሪፓራቶሪ አዲስ አበባ ተምሮ ካልገባ በስተቀር)፡፡
“የዘንድሮ ተማሪ ጥያቄዎች” ተብለው የተጠቀሱት
1.    ክሬዚ ዴይ/ ዋተር ዴይ/ ክራቫት (ጀንትል) ዴይ ይከበር፡- የድሮ ተማሪ ሲጀመር ጀንትል ስለሆነ የራሱን ቀን ማክበር አያስፈልገውም፡፡ የአሁን ተማሪ ደግሞ ክሬዚ ስለሆነ የራሱን ቀን ማክበር አያስፈልገውም፡፡ ከነዚህ መቅደም ያለባቸው ጥያቄዎች እንዳሉ ማንም አይክድም ነገር ግን እንዚህ ተማሪዎች ልጆች ናቸው በዛ ላይ ከዩኒቨርሲቲ እንደወጡ አብዛኞቹ የመንግስት (የቢሮም ኮብልስቶን መደርደርና መፍለጥም የመንግስት ስራዎች ስለሆኑ ነው) ስራ ላይ ነው የሚጠመዱት ስለዚህ አሁን ቺል አርገው ቢያልፉ ብዙ አያስቀይምም፡፡ ኧረ ደግሞ ማነው ከልክሎ የሚያውቀውና ነው ይከበር ብለው የሚጠይቁት፡፡
2.   የዳቦ ግራም ቀነሰ፡- እውነታቸውን ነው ታድያ አፈር ቅጠል የማይል ዳቦ እየሰጡ በሱም ብሶ ውስጡ ባዶ ሲሆን ይከፋል፡፡ ኮስት ሼሪንግ ተብሎ በአዲስ አበባ ኑሮ 300 ብር ብቻ እየተሰጠህ ከክፍለ ሀገር እንደ መምጣትህ ቤት ተከራይተህ ቀለብህን ችለህ ኑር ሲባል መጮህ ይነሰው እንዴ ጎበዝ የዳቦና ኮስት ሼሪንግ ጥያቄ አንድ ነው ብዬ ነው፡፡ ደግሞ የድሮ ተማሪ ዶሮ ወጥ እየበላ፣ ልብስና ጫማ እየተሰጠው አለፍ ሲልም የኪስ ገንዘብ እየተሰጠው እየተማረ ልቡን ጥጋብ ነፍቶት ነው መንግስት ላይ ቡራ ከረዩ የሚለው (ደሞ የዛ ዘመን መንግስት የዋህ ነው በጭስ አልሆን ካለው መሪውን መድፋት ካልሆነ እንደዚህ ዘመን ስርዓት የስናይፐር ጥይትን እንደ ነጭ ሽንኩርት አፍንጫህ ውስጥ አይከተውም)፡፡ ያሁን ተማሪ በኮስት ሼሪንግ (ማለትም በገንዘቡ) እየተማረ፣ እየተመገበ፣ እየኖረ ለምን ብሎ እየከፈለ አገልግሎት ይቀነስበታል፡፡
3.   ምግቡ አልጣፍጥ አለን፡- ይህ ጥያቄ ከላይኛው ጋር የተያያዘና ተመሳሳይ ነው፡፡ መልሱም አጭር ነው፤ በገንዘቡ ገዝቶ እየበላ ስለሆነ ጣፋጭ ምግብ ሊቀርብለት ይገባል፡፡
4.   የጎሳዬ ልጅ ተደበደበ፡- የተሸወዱት ነገር እንዲህ ብሎ የሚጠይቅ የለም፡፡ የእገሌ ልጅ ተደበደበ አይደለም እገሌ ተደበደበ ብትሉት እኔ ምን አገባኝ ትምህርት ቢዘጉልን ነበረ አሪፍ ካልተዘጋማ ከፈለገ ለምን እንደ ሽንኩርት ባናቱ ተክለው ወፌ ላላ አይገርፉትም ነው የሚላችሁ፡፡ እንዳጋጣሚ ሆኖ (አጋጣሚ አቃጣሪ ነው ይላል ጓደኛዬ) ይህን ጥያቄ ቢያነሱ እንኳ ልጁ ስለተደበደበ ሳይሆን የልጁን መደብደብ ምክንያት ሆኖ ትምህርት እንዲቋረጥ ነው፡፡ እመኑኝ፡፡
5.   የDSTv ካርድ በወቅቱ አልተገዛም፡- በነገራችን ላይ እኔ በአካል ካየኋቸው ዩኒቨርሲቲዎች ውስጥ የአዲስ አበባና የጅማ ዩኒቨርሲቲዎች ለተማሪዎች በነጻ ነው ኳስ የሚያሳዩት፤ እንደውም ጂማ ዩኒቨርሲቲ በየብሎኩ ነው ቴሌቪዥን ያለው መሰለኝ አዲሱ የኢንጂነሪንግ ዶርሚተሪዎች ጋር፡፡ ተማሪው በትርፍ ሰዓቱ ኳስ ቢከታተል አሪፍ ነው በርጫና ቅምቀማ ላይ ከሚሰየም፡፡ ጥያቄው ለምን ያያል እንዳልሆነ ይገባኛል የመጣበት አካባቢ የመሰረተ ልማት ግንባታ ይካሄድ ብሎ እንደ መጠየቅ ነገ እዛው ገጠር ጭለማ ውስጥ ተመልሶ እንሚገባ ረስቶት ስለ አንድ ነጫ ጭባ ቆዳ ገፊ (ለምሳሌ ክ. ሮናልዶ) እርግጫ መቋረጥ ይብከነከናል ነው፡፡ በአጭሩ ማለት የፈለጋችሁት ገብቶኛል ከኳስ ጋር በተገናኘ ብዙ ጊዜውን ከሚያሳልፍ ቢያነብ፣ ቢጠይቅ፣ ቢከራከር ለራሱም ለሀገሩም ይጠቅማል፡፡ እስማማለሁ፡፡
ባጠቃላይ ማለት የምፈልገው ትውልዱን በመውቀስ፣ የጥፋተኝነትና የሀሞተ ቢስነት ስሜት እንዲያድርበት በማድረግ ወደ ምንፈልገው አቅጣጫ መምራት እንችላለን ብላችሁ ካሰባችሁ ፉርሽ ናችሁ፡፡ ጭንጋፍ ሲባል ነው ወይስ አንበሳ ሲባል ነው ትውልዱ የሚበራታታው? መልሱን ለራሳችሁ፡፡ ደግሞ ከሁሉ በላይ የዩኒቨርሲቲ ተማሪ ስለሆነ ብቻ የግድ ተቃዋሚ መኾን አለበት ያለው ማነው? ከላይ እንደጠቀስኩት ቅንጅት ሲወዳደር እንዳለ ሽማግሌዎች ናቸው ለስልጣን የተወዳደሩት አደባባይ ወጥቶ የሞተው ግን አንዲት ጥቅም ያለገኘው/የማያገኘው (በመንግስትም በተ ቋሚዎችም) ወጣቱ ነው ስለዚህ የወጣቱን ደመ ሞቃትነት ተጠቅማችሁ ስልጣን መጨበት የምትፈልጉ አካላት በተለይም ዳያስፖራ ፓለቲከኞች እባካችሁ ለወጣቱ እዘኑለት (አሜሪካ ዱቅ ብላችሁ የግብፅን አብዮት ኢትዮጵያ ላይ እናስጀምር የምትሉ ቦለቲከኞች የግብፅ አብዮት የተጀመረው ውጭ ባሉ ግብጻውያን ሳይሆን ሀገር ውስጥ ባሉ ሁሉም ዜጎች ነው)፡፡
ዛሬ በጣም ብዙ ሊጻፍባቸው የሚችሉ ርዕሶች አንስቼ ያባከንኩ የሚመስላችሁ ሰዎች (እኔ እንደዛ ስለመሰለኝ ነው) እስቲ እናንተ በታትናችሁ ፃፉባቸው እኔም ሾጥ ካረገኝ እመለስባቸው ይሆናል፡፡ በተረፈ ግን ይሄ የፍሬዘር ምልከታ ስለሆነ የፈለኩትን በሚመቸኝ መልኩ ጽፌያለሁ፡፡ ቋንቋዬ ካልተመቻችሁ ይቅርታ ይሄ የዳንኤል ክብረት ብሎግ አይደለም እንዳልመፃደቅ (እንደ ስድብ እንዳይቆጥሩብኝ) ወይም የዳንኤል ብርሀኔ ብሎግ አይደለም የፖለቲካ/ዲፕሎማሲ ቃል የሚጠቀም፣ ይሄ የኔ ብሎግ ነው፣ እኔ ደግሞ እንደማወራው መጻፍ ነው የምፈልገው ብዙዎቻችን ስንጽፍ፣ በቴሌቪዥንና በሬድዮ ስናወራ አጻጻፋችንና አነጋገራችን ይለያያል ድራማና ፊልሞቻችንን ጨምሮ፡፡ እኔ ደሞ ይሄ ስታይላችሁ አይመቸኝም፣ እንደማወራው መጻፍ ስለምፈልግ፡፡ ይህች ፍንዳታ ምነው አለሁ አለሁ አለች ካላችሁኝ አቦ ይመቻችሁ እንዳለሁ ስላያችሁ፡፡ በነገራችን ላይ የፈለጋችሁትን ብትሉ ደስ እያለኝ እቀበላለሁ፡፡
ፍሬዘር ማሩ